ድህረ-ምረቃ ትምህርት በCOVID-19

በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ድህረ-ምረቃ ትምህርት ተጠናክሮ እንደቀጠለ ነው

 

በሙሉጎጃም አንዱዓለም

 

ዩኒቨርሲቲው በ"ኮቪድ 19" ምክንያት የመማር ማስተማሩን ሂደት በአካል ለአካል ማከናውን በማይቻልበት በዚህ ወቅት በየነ መረብን በመጠቀም ማስቀጠሉን  ዩኒቨርሲቲው  ኢንፎርሜሽን  ኮምኒኬሽን  ቴክኖሎጂ (ICT) ዳይሬክቶሬት አስታውቋል። 

 

የዩኒቨርሲቲው ኢንፎርሜሽን ኮምኒኬሽን ቴክኖሎጂ (ICT) ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ይበልጣል ማሩ የ"ኮቪድ 19" ወረርሸኝን ለመከላከል ሲባል ከትምህርት ሚኒስቴር በተሰጠው አቅጣጫ መሰረት በተለይ  ለሁለተኛና  ለሶስተኛ  ዲግሪ  ተማሪዎች  የመማር  ማስተማሩ  ሂደት  በበየነ  መረብ  የሚካሄድበት ስራ በተገቢው መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ በዋናነት  የሁለተኛና  የሦስተኛ  ዲግሪ ተማሪዎች በተያዘው መርሀ-ግብር እንዲያጠናቅቁ ለማድረግ ያለመ ሲሆን ለቅድመ- ምረቃ  ተማሪዎችም  በቤታቸው  ሊነበቡ  የሚችሉ ግባዓቶችን በማደርስ ላይ ይገኛል። 

 

ዳይሬክተሩ አክለውም  ወረርሽኙ ከመከሰቱ በፊትም ሆነ በኋላ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑንና ከዚህ በፊት ትኩረት ተነፍጎት የቆየው በክፍሉ የተሰራው የ "Learning Management System" (የትምህርት ማስተዳደሪያ ስርዓት) በአሁኑ ወቅት በበየነ መረብ የመማር ማስተማሩን ሂደት ለማከናወን ጉልህ አስተዋፅኦ በማበርከት ላይ መሁኑን  ተናግረዋል፡፡

 

በአሁኑ ወቅት  የዩኒቨርሲቲው መምህራን ለተማሪዎቻቸው የትምህርት መርጃ መሳሪ ለማስተላለፍ፣ለማስተማር፣ የቤት ስራዎችን ለመስጠት፡ ፈተናዎችን ለመፈተንና ለመሰል ተጓዳኝ ስራዎች የሚያግዝ ስልጠና በአካል መገናኘት ሳያስፈልግ  በ በየነ መረብ  እየተሰጡ መሆኑን ገልጸዋል።በተጨማሪም የሁለተኛና የሶስተኛ ዲግሪ ተማሪዎች ባሉበት ቦታ ሆነው የተለያዩ የቪዲዮ መገናኛዎችን በመጠቀም በየኮሌጆቻቸውና ፋኩልቲዎቻቸው የትልመ-ጥናት እና የመመረቂያ ጽሁፍ (ቴሲስ/ዲዘርቴሽን)  ተቋቁሞ (Defense) በማከናወን ላይ መሆናቸውን ዳይሪክተሩ ተናግረዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ዩኒቨርሲቲዉ የራሱን የVideo conference system ”https//meet.bdu.edu.et” አዘጋጅቶ እየተጠቀመ መሆኑን ዳይሬክተሩ አክለዉ ገልፀዋል፡፡